Friday, February 21, 2020

በመከራ ቀን እንዴት እንቁም?

- ዳዊት ወርቁ

ሐዋርያው ጳውሎስ ለኤፌሶን ሰዎች በመከራ ቀን እንዴት መቆም እንዳለባቸው ሲጽፍላቸው ምሳሌ
800px-centurion_2_boulogne_luc_viatour
ያደረገው ነገር ይገርመኛል:: ምሳሌው የአንድ የሮማ ወታደር ሙሉ ትጥቅን ነው:: በጊዜው የነበሩት የሮማ ታጣቂዎች ትጥቅን ከዘረዘረ በኋላ አንድ ክርስትያንም የእግዚአብሔር የጦር ዕቃ ሊኖረው ይገባል ይላል:: ምክንያቱ ደግሞ እኛም የምንዋጋቸው ጠላቶች አሉን:: ጠላቶቻችን ግን ሰዎች አይደሉም ይልቁንስ የክፉ መንፈሳዊ ሠራዊቶች ናቸው እንጂ:: እነሱም:-

1. አለቆችና ሥልጣናት
2. የጨለማ ዓለም ገዦች
3. በሰማያዊ ስፍራ የሚኖሩ የክፉ መንፈስ ሠራዊት ናቸው::
ጠላቶቻችሁ እነዚህ ናቸውና ሙሉ ትጥቅ ሊኖራችሁ ይገባል ነው የመልክቱ ጭብጥ::
የትኛውም ወታደር ራሱን ከጠላቱ ለሚወረወርበት ፍላጻ ለመከላከል ሙሉ ትጥቅ ሊታጠቅ ይገባል:: አንዱን ትጥቅ ቢያጎድል ጠላት ክፍተት አግኝቶ መጠቀሙ ስለማይቀር:: ከዚያ በፊት ግን አንድ ወታደር ወደ ግንባር ከመሄዱ በፊት በቂ ሥልጠና ማግኘት አለበት::

በውትድርና ዓለም ያለፉ ሰዎች ሥለ ውትድርና ሥልጠና ሲናገሩ አፍን ያስከፍታሉ::
ጳውሎስ በዘመኑ የሮማ ወታደሮችን እያሰበ መልክቱን ሲጽፍ እኔ ደግሞ በኔ ዘመን ያሉትን ወታደሮች አስባለሁ:: በልጅነቴ ብዙ የአሜሪካን የጦርነት ፊልሞችን አይቻለሁ:: ታዲያ የአሜሪካ ወታደሮች የሚታጠቁት ትጥቅና የሰውነታቸው አቋም ሲታይ በርግጥም ወታደር መሆን ያስመኛል:: የትጥቃቸው ብዛት የሰውነታቸው ብርታት የሚገርም ነው::ነገር ግን የስልጠናቸው አይነትና ብዛት ሲታይ ደግሞ ወታደር የመሆን ምኞትን ይገላል:: በሌሊት እየተነሱ የሚሰሩት የአካል ብቃት: ከባድ ቦርሳ በጀርባቸው ተሸክመው የሚሮጡት ሩጫ፥ የሚወጡት ተራራ፥የሚወርዱት ቁልቁለት፥ የሚያልፉበት የእሳት ቀለበት የሚዘንብባቸው የጥይት ዝናብ ፥ ዚግዛግ እየሠሩ የሚያመልጡት ነገር . . . በርግጥም ሥልጠናቸው በራሱ ሌላ ዓለም ነው::
በሁሉም ነገር ብቁ ሆኖ የተገኘ ወታደር ወደ ጦር ግንባር ከመሄዱ በፊት  የሚከተሉትን ትጥቅ ሊያሟላ የግድ ነው::

1. የደንብ ልብስ (Uniform)
አንድ ዘመናዊ አሜሪካዊ ወታደር ከነሙሉ ትጥቁ
soldier-uniform
ሐዋርያው እንደ ክርስቶስ ወታደር አንድ አማኝ የደንብ ልብስ  (በእሱ ጊዜ አጠራር) የጽድቅ ጥሩር ሊኖረው ይገባል ይላል:: የጽድቅ ጥሩር ምንድነው ? ብዬ ስፈልግ ያገኘሁት መልስ የሮማ ወታደሮች  እንደ ልብ መሰል ሥሥ ብልታቸውን የሚከላከልላቸው የትጥቅ ዓይነት ነው:: ደረታቸው አካባቢ የሚለብሱት ከነሃስ አሊያም ከብረት የሚሠራ ነው::

በዚህ ዘመን እንደ ሀገር መሪ ያሉ ሰዎች ከኮታቸው ሥር Iron vest (የብረት ሰደርያ) ይለብሳሉ:: በተለይም ዓደባባይ ሲወጡ:: ምክንያቱ አንድና አንድ ነው:: ከጠላት ጥይት እርሳስ ለማምለጥ::

ወታደር ከጠላቶቹ የሚለይበት አንደኛው ነገር የደንብ ልብስ ነው:: የልብሱ አስፈላጊነት አንድም ራሱን ከአካባቢውጋ የሚያመሳስልበት ሲሆን ደግሞም ከጠላቶቹ የሚለይበት ነው:: ልብሱ እንደየ አካባቢው ይለያያል:: ለምሳሌ ጦርነቱ ጫካ ውስጥ ከሆነ የወታደሩ ልብስ ቅጠልያ ወይም አረንጓዴ ይሆናል:: ወይ ደግሞ ጦርነቱ በረሃ ከሆነ አሸዋማ ይሆናል:: ይህ ስልት በተጨማሪ የጠላትን እይታ ለማሳሳት ነው ብዬ እገምታለሁ::

በሌላ አረዳድ ደግሞ የአይሁድ ካህናት ደረታቸውን ላይ የሚያደርጉት የደንብ ልብስ አለ:: ሐዋርያው የጽድቅ ጥሩር የሚለው ያንን የሚያመለክት ነው የሚሉም ሰዎች አሉ:: ምክንያቱም በብሉይ ኪዳን ዘመን ከሰው ሁሉ ተለይቶ ጻድቅ የሚባለው ካህኑ ስለነበረ ደረቱ ላይ የሚለብሰው ምልክት የጽድቅ ጥሩር ነው:: ሰው ሁሉ ያንን ምልክት ሲያይ ካህን መሆኑን  በቀላሉ ይረዳል:: ካህኑ ደረቱ ላይ በሚለብሰው የጽድቅ ጥሩር ይለያል::

እኛ ግን የጽድቅ ጥሩራችን ኢየሱስ ነው:: ኢየሱስን የለበሰ ሁሉ ካህን ነው:: ጠላትም በቀላሉ ይለየዋል:: መለያችን ጽድቃችን:: የማዕረግ ልብሳችን:: በርግጥም ጽድቃችን ክርስቶስ ነው:: ከጠላት የምናመልጥበት የማምለጫ ተራራችን የመማጸኛ ከተማችን ኢየሱስ ነው:: ኢየሱስን ያልለበሰ ሰው ከክፉው የሚላክበትን ሽንገላና ተቃውሞ መቋቋም አይችልም:: በክፉውም ቀን መቆም አይችልም:: ስለዚህ በክፉው ቀን ሁሉንም ተቋቋምነን ለማለፍ የጽድቅ ልብስ ልንለብስ ይገባል:: እርሱም ኢየሱስ ነው::
(ይቀጥላል)

No comments:

Post a Comment

ያልተዘራ አይታጨድም

- ዳዊት ወርቁ ባንድ ወቅት የሐብታም ቤተሰብ ልጅ ቤታቸው ድረስ እየሄድኩ ከመደበኛ ትምህርቷ ባሻገር በትርፍ ጊዜዋ ሳስጠናት ያጋጠመኝ እንዲህ ነው፡፡ የማስጠናት ልጅ ገና የሁለተኛ ክፍል ተማሪ ስትሆን፣ አዲስ አበባ ከተማች...