Thursday, December 19, 2024

ያልተዘራ አይታጨድም


- ዳዊት ወርቁ

ባንድ ወቅት የሐብታም ቤተሰብ ልጅ ቤታቸው ድረስ እየሄድኩ ከመደበኛ ትምህርቷ ባሻገር በትርፍ ጊዜዋ ሳስጠናት ያጋጠመኝ እንዲህ ነው፡፡
የማስጠናት ልጅ ገና የሁለተኛ ክፍል ተማሪ ስትሆን፣ አዲስ አበባ ከተማች ውስጥ በሚገኝ ዝነኛና የሐብታምና ባለሥልጣናት ልጆች ከሚማሩበት ትምሕርት ቤት ውስጥ ትማራለች፣ ወላጆቿ የተረፋቸው ናቸውና፡፡
ልጅቱ በተፈጥሮ የታደለችው ብሩህ አእምሮ ሲኖራት፣ ገና ከጅማሬው የምታስባቸው ነገሮችና የእንግሊዘኛ ቋንቋ ክህሎቷ የሚገርም ነበረ፡፡ ምንም እንኳ ገና የሁለተኛ ክፍል ተማሪ ብትሆንም ቅሉ፣ አመጋገቧ የተመጣጠነ ስለሆነ ሰውነቷ ያለ እድሜዋ አሳጥቷል:፡፡ ባጭሩ የአስራ ሁለት አመት ልጅ ሆና ሳለ፣ ለአቅመ ሔዋን የደረሰች ኮረዳ ትመስላለች፡፡ ይሁንና ወንድ ስታይ፣ (እኔ አስጠኚዋን ጨምሮ) አንዳንድ ድንበር የዘለሉ ባህሪያት (ታላላቆቿ እንደሚያደርጉት) ታሳይ ነበርና በጊዜው የነበረው ሁናቴዋ አደጋ ላይ እንዳለ ያመላክታል፡፡
ትዝ ይለኛል በጊዜው ቲቪ አፍሪካ በሚባል ቴሌቪዢን ጣቢያ ላይ “ላቪንግ” የሚል ፊልም ይተላለፍ ስለነበረ ልጅቱ በፊልሙ አለቅጥ ተነድፋ ኖሮ ሱሰኛ ሆናለች፡፡ ታዲያ ያቺ የሁለተኛ ክፍል ተማሪ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ መላ ነገሯ እየተለወጠ ሲመጣ አስተውላለሁ፡፡ ለምሳሌ ላስጠናት በምሄድበት ሰዓት፣ ኩል ተኩላ፣ በቻፕስቲክ ከናፍሮቿን አውዝታ፣ አገኛታለሁ፤ ይባስ ብላም በማስጠናት ጊዜ በሐሳብ ማዕበል ጭልጥ እያለች፣ ደግሞ ትምህርቱን ይዛው እንደሆነና እንዳልሆነ ስጠይቃት ደርሳ ድንግጥ እያለች፣ ሲላት እየተሽኮረመመች፣ እያፈረች መከራዬን አሳየችኝ፡፡
በወቅቱ ከዚያች አንድ ፍሬ ሕጻን የማይጠበቅ ባሕርይ ነውና ሁናቴዋ እንዲያው ሁሉን ለማወቅ መሻት የመጣ እንጂ ፈጽሞ ሌላ ነገር አልመሰለኝም፡፡ ይሁንና ስለፍቅር እንድተርክላት፣ ስለወንድና ሴት ተፈጥሮ እንዳወራላት፣ ስለ እራሴ ግላዊ ሕይወት እንድዘበዝብላት ግድ ትለኝ ጀመር፡፡ እንዲያውም አንድ ቀን፣
"Mister, do you know I am the only girl in our class who doesn’t have a boy friend?" ትለኛለች::
"No, I don’t know." እየደነገጥሁ::
"I am the only lonely girl." እንባዋ ባይኗ ግጥም ብሎ ካሁን አሁን እንደ ሐምሌ ዝናብ መጣሁ መጣሁ እያለ፤
What about the rest of the class?
They all have, but me. እንባዋ አሻፈረኝ ብሎ ግድቡን በመጣስ በጉንጮቿ ላይ ኩልል እያለ::
How it could be? አንቺኮ ገና ልጅ ነሽ፣ በዚያ ላይ ገና…
No, don’t say like that Mr. please? አቋረጠችኝ፤
Listen to me Sara (ስሟ ተለውጧል) when you become a big girl, like your older sister, you will have your own boy friend, but this is not the right time. And the only thing that what everybody expecting from you is just focusing on your school.
እንዲያም ሆኖ ምክሬ በጥቁር ድንጋይ ላይ ውሃ እንደ ማፍሰስ ከንቱ ሆኖ ቀረ::
ሲውል ሲያድርም ያቺ ጎበዝ ተማሪ የፈተና ውጤቷ እንደ መንገደኛ ስንቅ እየቀለለ እየቀለለ ሲመጣ አንድ ቀን እናቷን ጠራኋቸውና፣
“ልጅዎ እየደከመችብኝ ነው”
“ምን ማለት ነው?”
“በትምሕርቷ እየወረደች ነው”
“አንተ እያለህ እንዴት ይሆናል? የቀጠርንህ ለእንደዚህ አይነት ችግር መስሎኝ”
“ልክ ነው፤ የእኔ ርዳታ ግን ማስጠናት የቤት ስራዎቿንና አሳይመንቶቿን በጊዜ መስራት አለመስራቷን መቆጣጠርና ማሰራት እንጂ የባህርይ ለውጥ መቆጣጠር አይመስለኝም ”
“ልጃችን ባህሪዋ ተለውጧል እያልክ ነው?”
“አዎ በጣም፡፡ በእሷ እድሜ የማይታዩ ባህሪያት አይባታለሁ፡፡ ይህ ደግሞ የቤተሰብ ክትትልና አስተዳደግ ብሎም ለዕድሜዋ ተገቢ ያልሆነ ፊልም ተጽእኖ ይመስለኛል፣ እሷም ራሷ ቲቪ አፍሪካ ላይ ላቪንግ የሚለውን ፊልም በጣም እንደምትወደውና እንደምትከታተለው አልሸሸገችኝም፣ ስለዚህ ቢያንስ ቢያንስ ይህቺ ልጅ ይህን ፊልም ባታይ መልካም ነው”
እናትየው ምክሬ ብዙም ቅም አላላቸው፡፡ እንደሚታወቀው እንደ ብዙ ሐብታም ቤተሰብ፣ እዚያም ቤተሰብ ውስጥ አጓጉል ነፃነትና፣ ግዴታ አልባ መብት ያለቅጥ ተንሰራፍቶ ይታይ ነበር፡፡ ልጆቹ እላፊ ሄደው በዕድሜያቸው ያልተገባ ነገር ቢያደርጉ፣ ግሳፄ እንኳ ከስንት አንድ ነው የሚያገኙት እንኳን ቅጣት፡፡
የማታ ማታ ያቺ የደረጃ ተማሪ የነበረች ልጅ አይወርዱ መሽቆልቆል አሽቆልቁላ ከዕለታት አንድ ቀን እናቷ የትምሕርትቤት ሪፖርት ካርዷን ይዘው፣
“ይኼውልህ እንግዲህ ያንተ ውጤት አየኸው?! አንተ እያለህ ልጄ እንዲህ አይነት ውጤት ማምጣት አልነበረባትም” ሲሉኝ፣ የፈራሁትና የጠበቅሁት በመሆኑ ብዙም ሳልደነቅ፣
“አዩ ባለፈው ጊዜ ያስጠነቀኩዎ እንዲህ ዓይነት ነገር እንዳይከሰት ነበር፤ አሁን ግን የተፈራው ነገር ደርሷል፡፡ ለማንኛውም ግን የችግሩ መንስዔ እኔ ሆኜ በመታየቴ አዝናለሁ፡፡ ምክንያቱም ለልጃችሁ ውጤት መበላሸት ተጠያቂው፣ የእናንተ ቁጥጥር መላላት ነው፣ ልጅቱ እድሜዋ የማይፈቅዱላትን ፊልሞች ስትመለከትና በዚያ ተነድታ ስትወሰድ ዝም ብላችሁ አይታችኋልና” እያልኩ ራሴን ለማስመለጥ የቻልኩትን ያህል ብጥርም፣ ውጤት እንዳልቀናው የእግር ኳስ አሰልጣኝ ከመባረር አልዳንኩም፡፡
አሁን አሁን አያሌ ወላጆች፣ ልጆች የፈለገ ጥፋትና የማይገባ ነገር ቢያደርጉ፣ ዝንባቸው እሽ “እንዲባል አይፈልጉም፤ በተለይም በዕውቀት በልጽገናል በሐብት ደርጅተናል የሚሉቱ፣ ዳይስፖራ ቀመስ ወላጆች፡፡ ምንድነው ምክንያታችሁ?” ሲባሉ፣ “የልጆቻችንን መብት ላለመንካት ነው” ይላሉ፡፡ ግን ግን የልጅም መብት ማክበር እንዲህ መረን እየለቀቁ ነው እንዴ? . . .
አንድ ጊዜ እንደውም የሰማሁት የአንድ ባለሐብት ልጅ በአባቱ ሽጉጥ እቃ እቃ ሲጫወት እንደ መብት ተቆጥሮለት ታልፏል አሉ፡፡ ሌላ ቤት ደግሞ ልጅ አባዬ ራበኝ ስላለ አፈር ብላ ተብሎ በኩርኩም ቁንጮው የሚላጭ ልጅ የትየለሌ ነው፡፡ ልጅ አግድም አደግ ሆኖ እንዳያድ ግን፣ ገና በብላቴናነቱ በአርጩሜ ሾጥ ቢደረግ፣ ክፋት የለውም፡፡
መልካም ሰብዕና ከመልካም ቤተሰብ እንደሚገኝ ሁሉ፣ መልካም ማኅበረሰብ ደግሞ የመልካም ቤተሰብ ውጤት ነው፡፡ ዛሬ በስልጣን ወንበሩ ላይ ያሉት መሪዎቻችን ወደድንም ጠላንም የቤተሰብና የማኅበረሰቡ ውጤቶች ናቸው፡፡ ሰው ያልዘራውን አያጭድምና፡፡ መሪን የሚቀርጸው ቤተሰብ ነው፣ ቀጥሎ ማኅበረሰብ ነው፡፡ ታዲያ መሪዎቻችን ከፉም ለሙም የቤተሰብና የማኅበረሰብ ውጤት በመሆናቸው፣ ቤተሰብ ጋ በደንብ ሊሠራ ይገባል፡፡
ተስፋ ገና ሳለች ልጅህን ገሥጽ፥ መሞቱንም አትሻ።
መጽሐፈ ምሳሌ 19፥18
ልጅህን ቅጣ ዕረፍትንም ይሰጥሃል፤ ለነፍስህም ተድላን ይሰጣታል።
መጽሐፈ ምሳሌ 29፥17
Like
Comment
Share

Friday, February 21, 2020

በመከራ ቀን እንዴት እንቁም?

- ዳዊት ወርቁ

ሐዋርያው ጳውሎስ ለኤፌሶን ሰዎች በመከራ ቀን እንዴት መቆም እንዳለባቸው ሲጽፍላቸው ምሳሌ
800px-centurion_2_boulogne_luc_viatour
ያደረገው ነገር ይገርመኛል:: ምሳሌው የአንድ የሮማ ወታደር ሙሉ ትጥቅን ነው:: በጊዜው የነበሩት የሮማ ታጣቂዎች ትጥቅን ከዘረዘረ በኋላ አንድ ክርስትያንም የእግዚአብሔር የጦር ዕቃ ሊኖረው ይገባል ይላል:: ምክንያቱ ደግሞ እኛም የምንዋጋቸው ጠላቶች አሉን:: ጠላቶቻችን ግን ሰዎች አይደሉም ይልቁንስ የክፉ መንፈሳዊ ሠራዊቶች ናቸው እንጂ:: እነሱም:-

1. አለቆችና ሥልጣናት
2. የጨለማ ዓለም ገዦች
3. በሰማያዊ ስፍራ የሚኖሩ የክፉ መንፈስ ሠራዊት ናቸው::
ጠላቶቻችሁ እነዚህ ናቸውና ሙሉ ትጥቅ ሊኖራችሁ ይገባል ነው የመልክቱ ጭብጥ::
የትኛውም ወታደር ራሱን ከጠላቱ ለሚወረወርበት ፍላጻ ለመከላከል ሙሉ ትጥቅ ሊታጠቅ ይገባል:: አንዱን ትጥቅ ቢያጎድል ጠላት ክፍተት አግኝቶ መጠቀሙ ስለማይቀር:: ከዚያ በፊት ግን አንድ ወታደር ወደ ግንባር ከመሄዱ በፊት በቂ ሥልጠና ማግኘት አለበት::

በውትድርና ዓለም ያለፉ ሰዎች ሥለ ውትድርና ሥልጠና ሲናገሩ አፍን ያስከፍታሉ::
ጳውሎስ በዘመኑ የሮማ ወታደሮችን እያሰበ መልክቱን ሲጽፍ እኔ ደግሞ በኔ ዘመን ያሉትን ወታደሮች አስባለሁ:: በልጅነቴ ብዙ የአሜሪካን የጦርነት ፊልሞችን አይቻለሁ:: ታዲያ የአሜሪካ ወታደሮች የሚታጠቁት ትጥቅና የሰውነታቸው አቋም ሲታይ በርግጥም ወታደር መሆን ያስመኛል:: የትጥቃቸው ብዛት የሰውነታቸው ብርታት የሚገርም ነው::ነገር ግን የስልጠናቸው አይነትና ብዛት ሲታይ ደግሞ ወታደር የመሆን ምኞትን ይገላል:: በሌሊት እየተነሱ የሚሰሩት የአካል ብቃት: ከባድ ቦርሳ በጀርባቸው ተሸክመው የሚሮጡት ሩጫ፥ የሚወጡት ተራራ፥የሚወርዱት ቁልቁለት፥ የሚያልፉበት የእሳት ቀለበት የሚዘንብባቸው የጥይት ዝናብ ፥ ዚግዛግ እየሠሩ የሚያመልጡት ነገር . . . በርግጥም ሥልጠናቸው በራሱ ሌላ ዓለም ነው::
በሁሉም ነገር ብቁ ሆኖ የተገኘ ወታደር ወደ ጦር ግንባር ከመሄዱ በፊት  የሚከተሉትን ትጥቅ ሊያሟላ የግድ ነው::

1. የደንብ ልብስ (Uniform)
አንድ ዘመናዊ አሜሪካዊ ወታደር ከነሙሉ ትጥቁ
soldier-uniform
ሐዋርያው እንደ ክርስቶስ ወታደር አንድ አማኝ የደንብ ልብስ  (በእሱ ጊዜ አጠራር) የጽድቅ ጥሩር ሊኖረው ይገባል ይላል:: የጽድቅ ጥሩር ምንድነው ? ብዬ ስፈልግ ያገኘሁት መልስ የሮማ ወታደሮች  እንደ ልብ መሰል ሥሥ ብልታቸውን የሚከላከልላቸው የትጥቅ ዓይነት ነው:: ደረታቸው አካባቢ የሚለብሱት ከነሃስ አሊያም ከብረት የሚሠራ ነው::

በዚህ ዘመን እንደ ሀገር መሪ ያሉ ሰዎች ከኮታቸው ሥር Iron vest (የብረት ሰደርያ) ይለብሳሉ:: በተለይም ዓደባባይ ሲወጡ:: ምክንያቱ አንድና አንድ ነው:: ከጠላት ጥይት እርሳስ ለማምለጥ::

ወታደር ከጠላቶቹ የሚለይበት አንደኛው ነገር የደንብ ልብስ ነው:: የልብሱ አስፈላጊነት አንድም ራሱን ከአካባቢውጋ የሚያመሳስልበት ሲሆን ደግሞም ከጠላቶቹ የሚለይበት ነው:: ልብሱ እንደየ አካባቢው ይለያያል:: ለምሳሌ ጦርነቱ ጫካ ውስጥ ከሆነ የወታደሩ ልብስ ቅጠልያ ወይም አረንጓዴ ይሆናል:: ወይ ደግሞ ጦርነቱ በረሃ ከሆነ አሸዋማ ይሆናል:: ይህ ስልት በተጨማሪ የጠላትን እይታ ለማሳሳት ነው ብዬ እገምታለሁ::

በሌላ አረዳድ ደግሞ የአይሁድ ካህናት ደረታቸውን ላይ የሚያደርጉት የደንብ ልብስ አለ:: ሐዋርያው የጽድቅ ጥሩር የሚለው ያንን የሚያመለክት ነው የሚሉም ሰዎች አሉ:: ምክንያቱም በብሉይ ኪዳን ዘመን ከሰው ሁሉ ተለይቶ ጻድቅ የሚባለው ካህኑ ስለነበረ ደረቱ ላይ የሚለብሰው ምልክት የጽድቅ ጥሩር ነው:: ሰው ሁሉ ያንን ምልክት ሲያይ ካህን መሆኑን  በቀላሉ ይረዳል:: ካህኑ ደረቱ ላይ በሚለብሰው የጽድቅ ጥሩር ይለያል::

እኛ ግን የጽድቅ ጥሩራችን ኢየሱስ ነው:: ኢየሱስን የለበሰ ሁሉ ካህን ነው:: ጠላትም በቀላሉ ይለየዋል:: መለያችን ጽድቃችን:: የማዕረግ ልብሳችን:: በርግጥም ጽድቃችን ክርስቶስ ነው:: ከጠላት የምናመልጥበት የማምለጫ ተራራችን የመማጸኛ ከተማችን ኢየሱስ ነው:: ኢየሱስን ያልለበሰ ሰው ከክፉው የሚላክበትን ሽንገላና ተቃውሞ መቋቋም አይችልም:: በክፉውም ቀን መቆም አይችልም:: ስለዚህ በክፉው ቀን ሁሉንም ተቋቋምነን ለማለፍ የጽድቅ ልብስ ልንለብስ ይገባል:: እርሱም ኢየሱስ ነው::
(ይቀጥላል)

ያልተዘራ አይታጨድም

- ዳዊት ወርቁ ባንድ ወቅት የሐብታም ቤተሰብ ልጅ ቤታቸው ድረስ እየሄድኩ ከመደበኛ ትምህርቷ ባሻገር በትርፍ ጊዜዋ ሳስጠናት ያጋጠመኝ እንዲህ ነው፡፡ የማስጠናት ልጅ ገና የሁለተኛ ክፍል ተማሪ ስትሆን፣ አዲስ አበባ ከተማች...